ጥር 1/2018 ዓ.ም አዲስ አበባ፣

የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት እያካሄደ የሚገኘው የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ የምዕራፍ ሁለት የመስክ ስራ ላይ የሚሰማራውን የሰው ኃይል የሚያሰለጥኑ አሰልጣኞች ስልጠና በመላ ሀገሪቱ በተዘጋጁ 11 የስልጠና ማዕከላት ዛሬ ተጀመረ።

ስልጠናውን ከማዕከል በበይነ መረብ ያስጀመሩቱ የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር በከር ሻሌ ተቋማችን ላለፉት ሁለት ዓመታት ላከናወናቸው ታላላቅ ተግባራት ስኬት በትጋት በመስራትና ድጋፍ በማድረግ ለተሳተፉት በሙሉ ያላቸውን ምስጋና አቅርበው፤ የመካከለኛ ዘመን የስታቲስቲክስ ልማት ስትራቴጂ ዕቅድ የመጨረሻ ተግባር የሆነውን የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ድርጅቶች ቆጠራ የመጀመሪያ ምዕራፍ የመስክ ስራ በስኬት አጠናቀን ለሁለተኛ ዙር የመስክ ስራ ስንዘጋጅ የተገኙ ጥሩ ልምዶችን በማጠናከርና የነበሩትን ክፍተቶች በማረም የቆጠራውን የመጨረሻ ምዕራፍ በስኬት ለማጠናቀቅ በመስክ ስራው ላይ የሚሰራውን ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት ብቁ አሰልጣኞች አስፈላጊ መሆናቸውን በሚገባ በመረዳት ስልጠናውን በከፍተኛ ዲሲፕሊን ትጋት በመከታተል ለቀጣይ ቁልፍ ተግባር መዘጋጀት እንደሚገባቸው የስራ መመሪያ በመስጠት ስልጠናውን አስጀምረዋል።


