
ጥር 16/2018 ዓ.ም አዲስ አበባ፣
የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት በ2016 ዓ.ም ያካሄደውን አምስተኛ ዙር የኢትዮጵያ ስነ-ህዝብና ጤና ጥናት የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርት ውጤት የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፣ የጤና ሚኒስትር፣ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ሚኒስትር፣ ዓለም አቀፍና ሀገር አቀፍ አጋር ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ለተጠቃሚዎች ይፋ አደረገ።

በስርጭት መድረኩ ላይ የተገኙት የጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ዶ/ር መቅደስ ዳባ የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት በብዙ ችግሮች ውስጥ አልፎ ለሀገራችን የጤና ዘርፍ ቁልፍ አመላካች የሆነውን የዚህ ጥናት ውጤት ለተጠቃሚዎች ይፋ ማድረግ ላይ በማድረሱ ምስጋናቸውን አቅርበው በጤናው ዘርፉ ለሚካሄዱት የሪፎርም አጀንዳዎችን ዕውን ለማድረግ ከጥናቱ የሚገኙ መረጃዎች ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳላቸው ገልፀዋል።

ተቋማቸው ከሚሰራቸው የእናቶች፣ ህፃናትና ከስርዓተ ፆታ ጋር የተያያዙ ስራዎች ከጥናቱ የሚገኙ መረጃዎችና ለእናቶችና ለህፃናት ምቹ ሀገር እንድትኖረን መንግስት ለሚሰራቸው የዘርፉ ዋና ዋና ተግባራቶች ቁልፍ ፋይዳ እንዳላቸው የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬ ተናግረዋል።
ስርጭቱን በይፋ ያስጀመሩት የፕላንና ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ክብርት ዶ/ር ፍፁም አሰፋ ስራው እንዲክሳካ መንግስት መረጃን እንደአንድ ቁልፍ ልማት በመመልከት ጥናቱ ተጀምሮ እስከሚጠናቀቅ ድረስ አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረጉን ገልፀው፤ ይህ ስራ ከተቋሙ አመራርና ሰራተኞች ውጪ እውን ስለማይሆን የተቋሙ አመራርና ሰራተኞች ስራው እንዲሳካ ላደርጉት ትጋትና ጥረት ምስጋናቸው አቅርበው ከዛሬው ዕለት ጀምሮ የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርት ውጤት ለተጠቃሚዎች መሰራጨቱን ይፋ አድርገዋል።

መረጃው ቁጥር ብቻ ሳይሆን የህዝባችን ድምፅ ነው ያሉት የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ክቡር ዶ/ር በከር ሻሌ በዚህ ስራ ውስጥ ለተሳተፉ አመራር፣ ሰራተኞችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ምስጋናቸውን ገልፀው የዛሬው መድረክ ከመረጃ ስርጭት ባለፈ ጠንካራ የሆነ አጋርነት የምንፈጥርበት መድረክ ነው ሲሉ ገልጸዋል።

ጥናቱ በዋናነት በጨቅላ ህፃናትና እናቶች ጤና ላይ አመላካች የሆኑ የወሊድ ምጣኔናና የቤተሰብ እቅድ አጠቃቀም፣ ስለክትባት አወሳሰድ፣ እናቶች ከወሊድ በፊትና በኋላ የሚደረግላቸው የጤና እንክብካቤ፣ ኤች አይ ቪ ስርጭት፣ የህፃናት መቀንጨርና አመጋገብን የሚያሳዩ አመላካቾች እንደሚገኙበት ከቀረበው ገለፃ ለመረዳት ተችሏል።



