
ሐምሌ 29/2017 ዓ.ም አዲስ አበባ፣
የዓለም አቀፍ ስነ-ሕዝብ ፈንድ የኢትዮጵያ ቫይታል ስታቲስቲክስ መረጃ አሰባሰብና ሲቪል ምዝገባ ስርዓትን ለማዘመን እየተከናወኑ የሚገኙትን የሪፎርም ስራዎችን ለማጠናከር የሚያግዙ 17 ዴስክቶፕ ኮምፒውተሮች ድጋፍ ለኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት አስረከበ።

በርክክብ መርሀ ግብሩ ላይ የተገኙት የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር ክቡር ዶ/ር በከር ሻሌ የኢትዮጵያ መንግስት ዜጎች ከልደት እስከ ሞት የሚኖራቸውን መረጃ በአግባቡ በመሰብሰብ፣ በማደራጀትና ተንትኖ ለስነ-ሕዝብ የልማት ፖሊስና ዕቅዶች ግብዓትነት እንዲሁም ለዜጎች የተሳለጠ የማንናት መረጃ አገልግሎትለመስጠት የሚያስችል የቫይታል ስታቲስቲክስ መረጃና የሲቪል ምዝገባ ስርዓቶችን በመቅረጽናተቋማትን እስከ ታችኛው አስተዳደራዊ እርከን በማደራጀት ተግባራዊ እያደረገ እንደሚገኝ አንስተው ዛሬ በዓለም አቀፍ ስነ-ሕዝብ ፈንድ (UNFPA)የተደረገው የኮምፒውተር ድጋፍም በሀገሪቱ የቫይታል ስታቲስቲክስ መረጃና የሲቪል ምዝገባን መሉ በሙሉ ወደ ዲጂታል የመረጃ አሰባሰብና የምዝገባ ስርዓት ለመሻገጋር በመንግስት እየተደረጉ የሚገኙትን ጥረቶች ለመሳካት የሚያግዝ መሆኑን ጠቅሰው ድርጅቱ ላደረገው ድጋፍ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።


የዓለም አቀፍ ስነ-ሕዝብ ፈንድ (UNFPA) በኢትዮጵያ ተወካይ ሚስተር ታይዎ ኦልዮሚ ድርጅታቸው በሀገር አቀፍ ደረጃ ቅድሚያ የሚሰጣቸው የሲቪል ምዝገባ ስርዓቶችን ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን ገልፀው፤ ይህ ድጋፍ በኢትዮጵያ ጠንካራ የሲቪል ምዝገባና የቫይታል ስታቲስቲክስ መረጃ አሰባሰብ ስርዓት እንዲኖር ለማገዝ መሆኑን ገልፀዋል። በድጋፍ የተገኙት ዴስክቶፕ ኮምፒውተሮች ለተቋሙ 26 ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች የሚበረከት ይሆናል።



