
ሰኔ 10/2017 ዓ.ም አዲስ አበባ፣
የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የስርዓተ ፆታና የአካል ጉዳተኞች ስታቲስቲክስ መረጃዎችን በጥናት፣ በቆጠራና በአስተዳደራዊ መዛግብት መረጃዎች ለማካተት የሚያስችል መመሪያ ላይ ከተቋሙ መሪ ስራ አስፈፃሚዎች ጋር ውይይት አደረገ።
በውይይት መድረኩ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት የስነ-ሕዝብና ማህበራዊ ስታቲስቲክስ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ አይናለም ተሻገር የስርዓተ ፆታና የአካል ጉዳተኞች ስታቲስቲክስ የመረጃ ክፍተት መኖሩን ገልፀው ፤ ተቋሙ በሚያዘጋጃቸው የጥናትና ቆጠራ መረጃዎች ወጥና አለም አቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁ የስርዓተ ፆታና የአካል ጉዳተኞች ስታቲስቲክስ መረጃዎች እንዲካተቱ ለማስቻል መመሪያው መዘጋጀቱን አንስተው ሁሉም ጥናትና ቆጠራ የሚያከናውኑ የስራ ክፍሎች ለመመሪያው ግብዓት የሚሆኑ ሀሳቦች እንዲሰጡ የተዘጋጀ መሆኑን ገልፀዋል።

የስርዓተ ፆታ፣ የአካል ጉዳተኝነት ስታቲስቲክስ መረጃዎችን ከጥናትና ቆጠራ በተጨማሪ ከሌሎች አማራጭ የመረጃ ምንጮች ከተቋማት፣ ከማህበረሰብ ክፍሎችና ከግለሰቦች ከሚሰበሰቡ መረጃዎች (citizen Generated data) ላይ ማግኘት እንደሚቻል ተጠቅሶ የተዘጋጁት መመሪያዎች በስራ ክፍሉ መሪ ስራ አስፈፃሚና ከፍተኛ ባለሙያዎች ቀርበው ውይይት የተደረገባቸው ሲሆን ከተሳታፊዎች የተነሱ ሀሳብና አስተያየቶች እንደግብዓት ተወስደዋል።

በመድረኩ ማጠቃለያ የስነ-ሕዝብና ማህበራዊ ስታቲስቲክስ ዘርፍ ምክትል ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ አይናለም ተሻገር የተነሱትን ሃሳብና አስተያየቶች በማካተት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተጨማሪ ውይይቶች ተደርገው መመሪያው ስራ ላይ እንዲውል ቀጣይ የስራ አቅጣጫ በመስጠት ውይይቱ ተጠናቋል።