
መጋቢት 15/2018 ዓ.ም አዳማ፣
የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የ2018 ዓ.ም የንግድ እርሻዎች እና የሌሎች ድርጅቶችና ተቋማት እርሻ ጥናት የመረጃ ሰብሳቢዎችና ተቆጣጣሪዎች ስልጠና እየሰጠ ይገኛል።

በስልጠናው መክፈቻ ላይ የተገኙት የተቋሙ የስታቲስቲክስ ሜቶዶሎጂና ሲስተም ልማት ዘርፍ ም/ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ጀሚላ መሀመድ አሁን የሚካሄደው የንግድ እርሻዎች ጥናት በ2017 ዓ.ም ከተካሄደው ግዙፉ የግብርና ቆጠራ በተጠናቀቀበት ማግስት መሆኑን አንስተው የንግድ እርሻ ጥናቱ የ2017 ዓ.ም የግብርና ቆጠራን አጠቃላይ ጽንሰ ሃሳብና የመረጃ አሰባሰብ ስነ-ዘዴ መሰረት አድርጎ እንደሚካሄድ ገልፀዋል። ም/ዋና ዳይሬክተሯ አክለውም ለዚህ ጥናት ከመስክ መረጃ ለመሰብሰብ የምትሰማሩ መረጃ ሰብሳቢዎችና ተቆጣጣሪዎች ስልጠናውን በትኩረት በመከታተል ጥራት ያለው መረጃ እንድትሰበስቡ ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።

ስለጥናቱ አጠቃላይ ገለጻ ያደረጉት የግብርና ስታቲስቲክስ መሪ ስራ አስፈፃሚ አቶ አብዱላዚዝ ሽፋ የንግድ እርሻዎች ጥናት ስናካሂድ ከግብርና ቆጠራ ያገኘናቸውን ልምዶች እንደግብዓት በመጠቀም ጥራቱን የጠበቀ የንግድ እርሻዎች መረጃ ለመሰብሰብ እንሰራለን ሲሉ ገልፀዋል።



ስልጠናው ከ26ቱ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቶች ለተወጣጡ 205 የሚሆኑ መረጃ ሰብሳቢዎችና ተቆጣጣሪዎች ለቀጣይ አምስት ቀናት የሚሰጥ ይሆናል።
