መጋቢት 27/2018 ዓ.ም አዳማ፣

የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ከሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ጋር በመተባበር የመንግስት ሰራተኞችን መረጃ ለማረጋገጥ በስራው የሚሰማሩ መረጃ ሰብሳቢዎችን ለሚያሰለጥኑ አሰልጣኞች ሲሰጥ የቆየው ስልጠና ተጠናቀቀ።

በስልጠናው የመዝጊያ ፕሮግራም ላይ ተገኝተው የመድረኩን ማጠቃለያ ንግግር ያደረጉት የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር ክቡር ዶ/ር በከር ሻሌ በአሰልጣኞች ሥልጠና የተሳተፋችሁ የዩኒቨርሲቲ መምህራኖች፣ የዋናው መ/ቤትና ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ከፍተኛ የስታቲስቲክስ ባለሙያዎች፣ ከሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን የተውጣጣችሁ ከፍተኛ ባለሙያዎች ላለፉት ሰባት ቀናት በንድፈ ሀሳብና በተግባር በወሰዳችሁት ስልጠና በቂ እውቀትና ክህሎት እንዳገኛችሁና በቂ ቅድመ ዝግጅት እንዳደረጋችሁ በመረዳት በቀጣይ የምታሰለጥኗቸው መረጃ ሰብሳቢዎች በእውቀት ላይ ተመስርተው ጥራት ያለው የመረጃ ማረጋገጥ ስራውን እንዲያከናውኑ ማሰልጠን አለባችሁ ሲሉ የስራ አቅጣጫ ሰጥተዋል።

በመድረኩ የተገኙት የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ም/ኮሚሽነር ክቡር አቶ ሽብሩ አባዲማ የመንግስት ሰራተኞችን ፐርሶኔል መረጃ የማረጋገጥ ስራ ለሀገራችን ትልቅ ትርጉም ያለው መረጃ መሆኑን በመረዳት የዛሬው መድረክም በቀጣይ ለምናከናውናቸው ስራዎች ተግባብተን የምንሄድበትና በስራው ላይ የሚያጋጥሙንን ክፍተቶች በንግግር እየፈታን በሚፈለገው ጥራትና በተያዘለት የጊዜ ገደብ እንዲጠናቀቅ ኃላፊነታችሁን እንድትወጡ ሲሉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

ከሰልጣኞች ለተነሱ ቴክኒካል ጥያቄዎች በኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎት የስነ ህዝብና ማህበራዊ ስታቲስቲክስ ዘርፍ ም/ዋና ዳይሬክተር ክብርት ወ/ሮ አይናለም ተሻገርና በሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ም/ኮሚሽነር ክቡር አቶ ሽብሩ አባዲማ ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቶበት የስልጠና መድረኩ ተጠናቋል።





