
ሐምሌ 26/2017ዓ.ም፣
የፕላንና ልማት ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት በሲዳማ ክልላዊ መንግስት ደቡብ ሲዳማ ዞን ዳራ ወረዳ መጬሾ የገጠር ቀበሌ በመገኘት የ2017ዓ.ም የክረምት በጎ አድራጎት ስራ አስጀመሩ።

በገጠረ ቀበሌው ተገኝተው የክረምት በጎ አድራጎት ስራውን ያስጀመሩት የፕላንና ልማት ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ክብርት ወ/ሮ ጥሩማር አባተ የዚህ ዓመት የበጎ አድራጎት ስራ ባለፋት ዓመታት ከተሰሩት በተለየ መልኩ በክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴር ዶ/ር አብይ አህመድ በሀገራችን በገጠር የሚኖሩ ዜጎችን የአኗኗር ዘይቤ ለመለወጥ በወጠኑትን የገጠር አርሶ አደር የቤት አሰራር ኢኒሼቲቭ ሞዴል መሰረት በማድረግ የሚሰራ መሆኑን አንስተው በዚሁ መነሻ በ2017 ዓ.ም የክረምት በጎ አድራጎት ስራው በክልሉ በተመረጠው መጬሾ ገጠር ቀበሌ የአምስት አቅመ ደካማ ቤቶችን በአዲሱ የገጠር ነዋሪዎች የመኖሪያ ቤት ግንባታ ሞዴል መሰረት ገንብቶ ማስረከብ፣ለ1250 የአቅመ ደካማ ቤተሰብ ተማሪዎች ሙሉ የትምህርት ቁሳቁስ እንዲሁም ከ1000 በላይ ለምግብና ደን የሚውሉ ችግኞች ተከላ ስራ እንደሚከናወን በማስታወቅ ስራውን ለማስጀመር በክልሉ በነበራቸው ቆይታ በክልሉ፣ በዞኑና በወረዳው አመራሮችና በመጬሾ የገጠር ቀበሌ ነዋሪዎች ለተደረገላቸው ደማቅና ቤተሰባዊ አቀባበል በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱና ተጠሪ ተቋማቱ ስም የተሰማቸውን ከፍተኛ ደስታ በመግለፅ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

የሲዳማ ክልል የፕላንና ልማት ቢሮ ሀላፊ ዶ/ር አራርሶ ገረመው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱና ተጠሪ ተቋማቱ በክልላችን ደቡባዊ ዞን ዳራ ወረዳ መጬሾ ገጠር ቀበሌ የዚህ ዓመት የክረምት በጎ አድራጎት ለማከናወን ወስኖ በመካከላቸው በመገኘታቸው ያላቸውን ከፍተኛ አድናቆትና ምስጋና በማቅረብ የተጀመረው የበጎ አድራጎት ስራ በአጭር ጊዜ ተጠናቆ ለሚፈለገው አገለግሎት እንዲውል ክትትልና አስፈላጊውን ሁሉ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ገልፀዋል።



በበጎ አድራጎት ስራ ማስጀመሪያ መርሀ ግብሩ ላይ ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱና ተጠሪ ተቋማቱ የተውጣጡ ከ250 በላይ ሰራተኞች ተሳትፈዋል።






