
ሚያዝያ 22/2018 ዓ.ም አዲስ አበባ፣
የኢትዮጵያ ስታቲስቲክስ አገልግሎትና ከሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ጋር በመተባበር ለሚያካሂደው የመንግስት ሰራተኞች መረጃ ማረጋገጥ ስራ ላይ ለተቋሙ ሰራተኞች የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሀ ግብር ተካሄደ።

በመድረኩ ላይ ንግግር ያደረጉት የብቃትና የሰው ሀብት አስተዳደር ስራ አስፈፃሚ አቶ አወል አባመጫ የመንግስት ሰራተኞች መረጃ ማረጋገጥ ስራውን ለመጀመር የቅድመ ዝግጅት ተግባር መጠናቀቁን እና ተቋማችንም አንዱ የዚሁ አካል በመሆኑ መረጃ የማረጋገጥ ስራው በቋሚ የስራ መደብ ላይ ተቀጥረው የሚሰሩ ሰራተኞችን የሚመለከት መሆኑን ገልፀው፤ በተቋሙ ያሉ ሰራተኞችም ይህንን በመገንዘብ የሚያስፈልጉ መረጃዎችን እንዲያሟሉና መረጃ ሰብሳቢዎች በሚመጡ ጊዜ በአካል ተገኝተው አስፈላጊውን ሁሉ እንዲያደርጉ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።

በሀገር አቀፍ ደረጃ የሚካሄደው የመንግስት ሰራተኞች መረጃ የማረጋገጥ ስራ ዓላማ፣ ምን ዓይነት መረጃዎችን ይረጋገጣሉ፣ ከሰራተኛው ምን ይጠበቃል የሚለው ላይ ሰፊ ገለፃ ቀርቦ ግ ንዛቤ የተፈጠረ ሲሆን በገለፃው ላይ ለተነሱ ጥያቄዎች ምላሽና ማብራሪያ ተሰጥቷል።

